Warning: Declaration of Custom_Menu_Wizard_Walker::walk($elements, $max_depth) should be compatible with Walker::walk($elements, $max_depth, ...$args) in /home/bntcd7mezmpx/public_html/ethiopic.com/wp-content/plugins/custom-menu-wizard/include/class.walker.php on line 55

Warning: Declaration of Custom_Menu_Wizard_Sorter::walk($elements, $max_depth = 0) should be compatible with Walker::walk($elements, $max_depth, ...$args) in /home/bntcd7mezmpx/public_html/ethiopic.com/wp-content/plugins/custom-menu-wizard/include/class.sorter.php on line 60
Dr. Aberra Molla -
Warning: Use of undefined constant ddcf_custom_css_check - assumed 'ddcf_custom_css_check' (this will throw an Error in a future version of PHP) in /home/bntcd7mezmpx/public_html/ethiopic.com/wp-content/plugins/dd-contact-form/inc/functions.php on line 123

Dr. Aberra Molla

እናስተዋውቅዎ በሚለው ኣምዳችን የትምህርት ዕውቀታቸውንና የሥራ ልምዳቸውን በማጣመር ውድ ኣገራቸውን ለመርዳት ከፍተኛ ጥረት ያደረጉ ኢትዮጵያውያንን ኣቅማችንና ጊዜያችን በፈቀደልን ጊዜ ከሕብረሰባችን ጋር የምናስተዋውቅበት ኣምድ ነው። በእዚህ እትማችን በከፍተኛ የትምህርት መደባቸው ባገኙት የዶክትሬት ዲግሪ ሳይወሰኑ ሌሎችንም የትምህርት ዘርፎች በመመርመር እናት ኣገራቸውንና ልጆችዋን በመርዳት ላይ የሚገኙትንና ተቀማችነታቸው በኮሎራዶ የሆኑትን ምሁር ዶክተር ኣበራ ሞላ ማንነት የሥራ ውጤትና የወደፊት እቅድ በተመለከተ ከዘገባው ሪፖርተራችን ደምሴ ኣጎናፍር ጋር ሙሉ ቃለ ምልልስ ይዘን ቀርበናል። መልካም ንባብ።

ዶ/ር ኣበራ ሞላ
ዘገባ፣ በመጀመሪያ ይኸንን ቃለ ምልልስ ለመስጠት ስለፈቀድክልን ኣመሰግናለሁ። ሙያህንና ያበረከትካቸውን ኣስተዋጽዎች ኣስመልክቶ ወዳሉኝ ጥያቄዎች ከመግባቴ በፊት ኣንባቢዎቻችን ስላንተ ማንነት ይረዱ ዘንድ ባጭሩ ስለሥራህ እንዲሁም ስላጠናኸው ትምህርትና ሥራ ልምድህ ብትገልጽልን?

ዶ/ር ኣበራ፦ እኔም ጥያቄዎችህን እንድመልስ ዕድሉ ስለተሰጠኝ ኣመስግናለሁ። ባለትዳርና የሦስት ልጆች ኣባት ነኝ። ላለፉት 33 ዓመታት የኖርኩትም ኮሎራዶ ነው። የተማርኩት የእንስሳት ሕክምና ሲሆን ከተመረቅኩም በኋላ ለጥቂት ዓመታት ሠርቼ ለተጨማሪ ትምህርት ኣሜሪካ ተልኬ ከኮሎራዶ እስቴት ዩኒቨርሲቲ ተመርቄኣለሁ። ለዲግሪዬም ማሟያ ምርምር ስሠራ የእንስሳት መድን መዳከምን የሚያስከትል መቋቋሚያ ዘዴ ኣግኝቼ በየዓመቱ የሚጠፋውን የብዙ ሚሊዮን ሕይወት ለማትረፍ ችያለሁ [1]። ለብዙ ዓመታት የተለያዩና ኣዳዲስ የበሽታ መከላከያ ክትባቶችን ሠርቻለሁ። በኣሁኑ ጊዜ በኣሜሪካ እርሻ ሚኒስቴር ውስጥ በሽታዎች ከምግብ እንስሳት ወደ ሰዎች እንዳይተላለፉ የሚቻልበትን መንገድ በመከታተል ላይ እገኛለሁ።

ዘገባ፣ ኢትዮጵያውያን በኤድስ ሕመም ተጠቅተው ሕይውታቸውን እንዳያጡ የሚለግሱ ምክሮችን ከረዥም ጊዜ ጀምሮ ስትለግስ ቆይተሃል። ለመሆኑ ተላላፊው የወፍ ወረርሽኝ ወይም ኤቪያን ፍሉ በመባል የሚታወቀው በሽታ ኣገራችን ኢትዮጵያን ያሰጋታል?

ዶ/ር ኣበራ፦እ.ኤ.ኣ. የ1976 ምርምሬ ስለ መድኅን መዳከም (ኢምዩንደፊሸንሲ) በመሆኑ ኤድስ[2] ኢትዮጵያ ውስጥ ሊያስከትል የሚችለውን ችግር ለመገመት በመቻሌ ሰዉ እንዲጠነቀቅ ከመናገርና ከመጻፍ ኣልተቆጠብኩም። በተለይ በ1988 ኤ.ዲ. ስለ ኤድስ ከእንግሊዝኛ በመተርጐምና [3] ዕውቀቴንም በመጠቀም በዓማርኛ የጻፍኩትን ኣራት ገጾች ጽሑፍ በ1991 ኢትዮጵያን ሪቪው መጽሔት ላይ ከማሳተሜ ሌላ ከ1997 ገደማ ጀምሮ ኢትዮፒክ.ኮም [4] ድረ ገጼ ላይ ኣለ። ስለ ኤድስ ያቀረብኩት ሲጀምር በመሆኑም በሽታው ያጠቃን ዕውቀቱ ጠፍቶን ብቻ ኣይደለም ባይ ነኝ። ይኸው ጽሑፍ በቅርቡ ዊኪፔዲያ ላይ ቀርቧል። ኣወን ኤቭያን ፍሉ (Avian Flu) ኢትዮጵያን እንደ ማንኛውም ኣገር ያሰጋታል። ይህ የወፍ ኢንፍሉኤንዛ ወይም የዶሮ ጉንፋን እያጠቃ ያለው ኣንዳንድ የሩቅ ምሥራቅ እስያ ኣገሮችን ቢሆንም ወደ ኤውሮጳና ኣፍሪቃ መስፋፋት ጀምሯል። እስካሁን በሽታው የገደላቸው ሰዎች ብዛት ከ300 ያነሱ ሲሆን በሽታውን ለመቆጣጠር ከ150 ሚሊዮን ዶሮዎች በላይ ተፈጅተዋል። ያለውም ዋና ስጋት ቫይረሱ ከታመመ ዶሮ ሰው ጭምር ስለሚይዝና እራሱንም መቀያየር ስለሚችል ቀስ በቀስ ጉንፋኑ ከሰው ወደ ሰው የመተላለፍ ችሎታ ኣፍርቶ ሕዝብ እንዳይፈጅ ነው። ከዚህ በፊት ኢንፍሉኤንዛ በመደጋገም በዓለም ላይ ብዙ ሚሊዮን ሕዝቦች ገድሏል። ስለዚህ ስለበሽታው ሕዝቡ በሚገባ ማወቅና መዘጋጀት ኣለበት። በሽታው ኣንድ ቦታ ያሉትን ዶሮዎች በ48 ሰዓታት ሊፈጅ ይችላል። ኣንዳንድ ኣእዋፍ ወደተለያዩ ኣገሮች ስለሚበሩ በሽታውን መከላከል ቀላል ባይሆንም የመከላከያ ክትባት ኣለ። ለሰው መድኃኒትና መከላከያ የመሥራትም ጥድፊያ ቀጥሏል። በብዛት የሞቱ ኣእዋፍ ሲታዩ ለባለሥልጥኖች መንገር እንጂ ኣለመነካካትና ድመቶች እንዳይበሏቸው መከላከል ያስፈልጋል። በሽታው ካለበት ኣገር ዶሮን ኣለማስገባትና የጓሮ ዶሮን ኩስ ማጸዳዳት ጠቃሚ ናቸው። ዶሮንና እንቁላልን ለመብላት በሚገባ ማብሰል ቫይረሱን ይገድለዋል። ስለዚህ በሽታ ወደፊት በሰፊው ለማቅረብ ዕቅድ ኣለኝ።

ዘገባ፣ ተቀዳሚ ሙያህ በሕክምና ዙሪያ ላይ ያተኮረ ሲሆን ነገር ግን የዛሬ 25 ዓመት ገደማ ዓማርኛና ሌሎች የኢትዮጵያ ቋንቋዎች ለኮምፕዩተር ቅንብር ብቃት ኖሯቸው እንዲዋሃዱ ለማድረግ የሚያስችል የቃላት ማቀነባበርያ ለመፍጠር የገፋፋህ ዓላማ ምንድነው?

ዶ/ር ኣበራ፦ፊደላችንን ከልጅነቴ ጀምሮ እወደዋለሁ። ኣምስተኛ ክፍል እያለሁ በችሎታዬ ይደነቁ ከነበሩት የጅማ ሰንበቴ ትምህርት ቤት ኣስተማሪዎቼ ወይዘሮ ኣዳነች ይግዛው ለሚባሉት ጥላ ያለው የዓማርኛ የጥልፍ ፊደል ስሠራ እንደነበረ ኣስታውሳለሁ። በኋላም የዓማርኛ የመኪና (ታይፕ) መጻፊያንም ሳይ ፊደሉ በመበጣጠሱና በመበላሸቱ ቅሬታ ነበረብኝ። እንግሊዝኛው በኮምፕዩተር መጻፍ ሲጀመር የሚሠራው በኣንድ የፊደል ገበታ ብቻ በመሆኑ ለግዕዝ እንዲጠቅም ኃይሉ እስኪሻሻል ጠብቄ በ1987 ኤ.ዲ. (፲፱፻፹ ዓ.ም.) ለመጀመሪያ ጊዜ የግዕዝ መጻፊያ ሥራዬን ኣቅርቤያለሁ [5]። ግዕዝን በኮምፕዩተር መጻፍ የቻልኩትም ፊደሎቹን ከስምንት የፊደል ገበታዎች በላይ ላይ በመበተን ነበር። ቴክኖሎጂው ሲጀምር ታግዬ የማተሚያ ቤቱን ዓይነት በኮምፕዩተር እንዲሠራበት ማድረግ ባልጀምር ኖሮ የግዕዝ ፊደል ተብሎ ወደ ኮምፕዩተርና የዓለም ፊደላት መደብ ውስጥ የሚገባው የዓማርኛ የጽሕፈት መኪናው ዓይነት ዓማርኛ ያልሆነው የቅጥልጥል ፊደል ነበር። ኣንዳንድ ኣዳዲስ ነገሮችን ኣንብበን የመፍጠር ችሎታ ያለን ሰዎች ቴክኖሎጅው ሲጀምር ሌሎች ሊሠሩልን የማይችሉትን ታግለን ኣብረን ካልጀመርን ብዙ ከተገሰገሰ በኋላ እንኳን ሊደረስበት የኣሠራሩ ደብዛ ስለሚጠፋ ታግያልሁ [6]

ዘገባ፣ ኣንተ የፈጠርከው የቃላት ማቀነባበርያ በወቅቱ በሰፊው ሥራ ላይ ይውል ከነበረው የመኪና ጽሕፈት መሣሪያ ተመስሎ የተሠራውን ኋላ ቀር የቅጥልጥል ፊደል ጽሕፈት ሙሉ በሙሉ እንዲጣል ማድረጉ በሰፊው ይነገራል። እስኪ ስለዚህ ጉዳይና በዚህ ሳቢያ ከሌሎች ሙያተኞችና ጠበብቶች ጋር የተነሳውን ያካሄድ ግጭቶች እንዲሁም ሌሎች ችግሮች ብታብራራልን?

ዶ/ር ኣበራ፦ እኔ ግዕዝ በኮምፕዩተር እንዲሠራ ስሞክር ቀደም ብዬ ማውጣት የምችለውን የዓማርኛ የመኪና መጻፊያውን ዓይነት በተለይ እ.ኤ.ኣ. ከ1985 ወዲህ ያወጡ ነበሩ። የእኔው ለገበያ ሲቀርብ እያንዳንዱ ፊደል ላይ ጭረትና ቀለበት የመሳሰሉትን በመጨመር የሚከተበው የቅጥልቅሉ የዓማርኛ የመኪና መጻፊያ ሳይሆን እያንዳንዱ ፊደል እራሱን የቻለና ትክክለኛውና በእጅ የምንጽፈው ወይም ማተሚያ ቤቶች የሚጠቀሙብት የግዕዝ ፊደል በመሆኑ ሌሎቹን ዋጋ ኣሳጣቸው።እንዲህም ሆኖ ትክክለኛው ተፈጥሯልን እንደግፍ እንደማለት የቅጥልጥሉን ኣሠራር በነፃ በመስጠትና በ1990 ለተቋቋመ ዩኒኮድ ለሚባል የዓለም ፊደላት ድርጅት በሓሰት የግዕዝ ፊደል [7] ብለው ኣቅርበው ብዙ ችግሮች ኣድርሰውብኛል። ለምሳሌ ያህል የዓማርኛ የታይፕ መጻፊያ ያለው የመርገጫዎች ብዛት ከመቶ ያነሱ ስለሆኑ ዓማርኛን ለመጻፍ ከመቶ ያነሱ ስፍራዎች በቂ ናቸው ብለው ለዩኒኮድ ኣቅርበዋል። ይኸንንም ተቃውሜና ጽፌ [8] ከእነሱ ተገላከልኩ ስል ደግሞ ሌሎች ትክክለኛዎቹን የዓማርኛ፣ ትግርኛና ኦሮምኛ ፊደላት ኣቅርበው የቀሩትን እንቀጣጥላለን ብለው ለሁለተኛ ጊዜ ያልተሟላ ፊደል እ.ኤ.ኣ. በ1993 ለዩኒኮድ ኣቀረቡ። ዩኒኮድንም ያልተሟሉ የግዕዝ ፊደላትን እንደገና ትቶ የተሟሉና ትክክለኛዎቹ የግዕዝ ፊደላት የዓለም የፊደል መደብ ውስጥ በቅርቡ (2002) ገብተዋል [9]። ግን ይህ የሆነው ሌሎቹ በቅጥልጥል እንዲገቡ የፈለጉት ከተሳካላቸውና ለግዕዝ ወደ 368 ግድም [10] ቦታ ከተመደበለትና ቦታው ከተዘጋበት በኋላ በመሆኑ የተተዉት የግዕዝ ፊደላት ከሌሎች ኣዳዲስ የዩኒኮድ ስፍራዎች በቅርቡ ዩኒኮድ ውስጥ ገብተዋል። የግዕዝ ፊደል፣ ኣኃዝና ምልክቶች ብዛታቸው ወደ 480 ስለሆኑ ያንን ያህል ቦታ ይመደብ ብዬ ብቻዬን ብታገልም ስላልተሳካልኝ ሌሎች በጀመሩት ጠንቅ ነው ዛሬ የግዕዝ ፊደላት ዩኒኮድ ውስጥ ተበጣጥሰው ሦስት ቦታ እንዲመደቡ የሆነው። እነዚህም ከኣንድ ቦታ ሊቀርቡ ይችሉ የነበሩት ዛሬ ግዕዝ፣ ተጨማሪ ግዕዝና ተራዛሚ ግዕዝ (Ethiopic, Supplemental Ethiopic, Extended Ethiopic) በሚል የፈጠራ ስም ተሰጥቷቸው ተበታትነው የቀረቡት። ይህም ለግዕዝ ውርደት ነው። እንዲህም ሆኖ ነገሩ ገብቷቸው ከእኔ ጋር ለእውነት የደከሙ ቢኖሩም ያልገባቸውና ዛሬም በቅጥልጥል የዓማርኛ የመኪና መጻፊያ ዓይነት ፊደላትም የሚጠቀሙ ኣሉ። ሥራዬንም ለማዳከም እኔ የሠራሁትን የግዕዝ ኣጠቃቀም ቀድተው ለመሸጥ ያልተሳካላቸውና በነፃም ሲበትኑ የነበሩ ኣሉ። የቅጥልጥሉን የዓማርኛ ፊደላት ለኮምፕዩተር ካቀረቡት ኣንዱ እውሸቱን ኣሻሽሎ ግዕዙን ኣቀረብኩ ማለት ጀምሯል። ይህም ዝምታና ግዴለሽነት ግዕዝ ላይ ያመጣው ሌላ ውርደት ነው። ከእዚህም ሌላ የእነዚህን ማወናበድ በመከተል የተለያዩ ፊደላት ኣቀማመጥ ያላቸው ወደ ሠላሳ የሚጠጉ የማይናበቡ መጻፊያዎች ቀርበው ሕዝቡን ሲያበሳጩት ከርመዋል። ያበላሹትም ፊደላቱን ብቻ ሳይሆን የኣከታተብ ፈጠራዬንም ነበር። ምክንያቱም የዓማርኛ የመኪና ኣጻጻፍ ለዓማርኛ በቂ ስላሆነና ኣሠራሩም ኋላ ቀርና ብዙ መርገጫዎችን መነካካትን የሚያስፈልግ በመሆኑ ወደ 480 ለሚጠጉት የግዕዝ ፊደላት፣ ኣኃዛትና ምልክቶች እያንዳንዱን ከሁለት መርገጫዎች ባላበለጡ የሚጻፍበትን ፈጠራዬንም ጭምር ነበር ያበላሹት።

ዘገባ፣ የኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርሲቲ የዓማርኛ ፊላት ይቀነሱ በማለት ኣንዳንድ ተደጋጋሚ ሆህያት እንዲቀሩ መወሰኑን ሰምተናል። ኮምፕዩተር ይህን ውሳኔ ይረዳል ወይስ ይጎዳል?

ዶ/ር ኣበራ፦ ትክክለኛ ሆህያትን ለማወቅ የሚያስችል መዝገበ ሆህያት እና መዝገበ ቃላት ስላሉ ኮምፕዩተር ተራድቷል። የኮምፕዩተር ኣንዱ ጥቅምም ቃላትን ከጽሑፍ ወይም ኢንተርኔት ለመፈለግ ነው። ጸሓፊዎች ቃሎቻቸውን በትክክለኛዎቹ፣ በተቀነሱ ወይም በተገኘው ፊደል መጻፍ ጀምረዋል። እነዚህን ቃላት ለማግኘት በሚጻፉባቸው ዓይነቶች ሁሉ መፈላለግ ስለሚያስፈልግ ፊደላቱን መቀነስ ሥራ ሳያስጨምር ኣልቀረም። ይህ ሰውን ሊያሰለችና ቋንቋውን ሊያዳክም ይችላል። ለምሳሌ ያህል “ሰረቀ” እና “ሠረቀ” የሚባሉት ቃላት ከግዕዝ የመጡ ስለሆነ ትክክለኛዎቹን ሆህያት ካልተጠቀምን ስሕተት ነው የሚሉ ኣሉ። ኣንዱን “ሰ” ብቻ ተጠቅመን ትክክለኛውን ትርጕም ከዓረፍተ ነገር ማግኘት መሻሻል ኣይደለም። የቃላት ኣመጣጥ ጥናት ኤቲሞሎጂ (Etymology) ይባላል። ይኸን ማወቅ ኣዳዲስ ቃላትን ለመፍጠር ይረዳል። ፈረንጆች ቃላት እንዳይበላሹ በእስፔሊንግ ጣጣ ሲቸገሩ እያየን ትክክለኛዎቹን ሆህያት እንደማስተማር የዓማርኛ እስፔሊንግ ጣጣ መጀመር ከጥቅሙ ይልቅ ጉዳቱ የሚያመዝን ይመስለኛል። ይቅሩ የተባሉትን ፊደላት እያስተማርን ኣትጠቀሙባቸው ማለትም ዓዋቂዎችን ማደናቆር ይመስላል። የግዕዝ ኣኃዞች እንዳይዳከሙ የግዕዝን ኣልቦ [11] (ዜሮ) በመሥራት ከ፩ እስከ ፱ ካሉት ጋር እንድንጠቀምባቸው ለሃያ ዓመታት ሳቀርብ የኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርስቲ ሲደግፍ ኣልሰማሁም። በኣሁኑ ጊዜ የግዕዝ ኣኃዞች ዩኒኮድ ውስጥ ያሉት በፊደልነት እንጂ በኣኃዝነት ኣይደለም። ማንም ዕውቀትን ማጥፋት ይችላል። መጨመር ግን ከምሁራን ከሚጠበቁት ኣንዱ ነው። ሰለዚህ ፊደል መቀነሱ ላይ ስናተኵር ቋንቋውን እንዳናዳክም ባይ ነኝ። የኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርስቲ (Addis Ababa University) ማድረግ ካለበት ኣንዱ የእራሱን ስም ትክክለኛ ስም በዓማርኛ (ኣዲስ ኣበባ ዩኒቨርስቲ) በማለት እንዲሁም በእንግሊዝኛ (Addis Abeba University) ብሎ ማረምና ማሳወቅ ይመስለኛል።

ዘገባ፣ ኣንዳንድ የመንግሥት ተቋማት፣ የግል ድርጅቶችና የኪነት ሰዎች እንዲሁም ግለሰቦች ኣዙረው ሳያስቡ ያለማመንታት የባእድ ቃላትን በተለይም እንግሊዝኛ ቃላትን ቋንቋችን ውስጥ እየዘነቁ ሲያጎድፉ ይስተዋላል። ለመሆኑ የፈጠርከው የኢትዮጵያ ቃላት ማቀነባበርያ ይህንን ነውርና ኣሳፋሪ የቃላት ድቀላና ብረዛ ኣሠራር ባሕል ለመቀየርና ብሎም ለማስወገድ በምን መልክ ይረዳል?

ዶ/ር ኣበራ፦ በርግጥ ጥሩ ጥያቄ ነው። ይሄ ጉዳይ እስካሁን ድረስ ቁርጠኛ መፍትሄ ያልተገኘለት ረዥም ጊዜ ያስቆጠረ ችግር ነው። ሳይታሰብበት እንግሊዝኛ እየከለሱ ዓማርኛን መናገርና መጻፍ እንዲሁም ሕዝባዊና መንግሥታዊ ተቋማት በቸልተኝነት በላቲን ቋንቋ በታጀቡ የመለያ ስሞች ማስተዋወቅንና መንግሥታዊ ገለጻዎችን ማድረግ በሰፊው የሚታይ ብሔራዊ ገጽታ ነው። በጣም የሚገርመው ለምሳሌ ኣንዳንድ ሰዎች የሚያወሩት ውስጥ በርከት ያሉ የእንግሊዝኛ ቃላት ስለሚጨምሩ እንግሊዝኛ የማያውቁ ስለ ጉዳዩ ስለማይገባቸው የሰው ጊዜ ያጠፋሉ። ከእነዚሁ ኣስመሳዮች በእንግሊዝኛ ኣውሩ ቢባሉ ደግሞ የባሰ ችግር ውስጥ የሚገቡ ኣይጠፉም። ለማንኛውም የዕውቀቱ መጀመሪያ ዋቤውን መጻፍና መናገር መሆኑ መታወቅ ስላለበት ኢንተርኔት መብት ስለሰጠን መጻፍና ማንበብን ማስፋፋት ይቻላል። በተጨማሪም መዝገበ ቃላትንና ትክክለኛ ሆህያትን በቀላሉ ማቅረብ ስለሚቻል ዕድሉ ኣለ። በቴክኖሎጂ መመንጠቅ የተነሳ ኣዳዲስ የእንግሊዝኛ ቃላትን በመተርጎም ማቅረብ ሳይጠቅም ኣይቀርም። እንዲህም ሆኖ እንግሊዝኛ ኣንስማ ማለት ሳይሆን እነ ቸርችና እስኩል የመሳሰሉትን ቃላት ዓማርኛ ውስጥ መቀላቀል አስፈላጊ ስላልሆነ ያልተማሩትን ማስተማር እንጂ የተማሩት መጥፎ ኣርኣያ መሆን ኣይጠቅምም። በኣንጻሩም የኢትዮጵያ ከፍተኛ የቋንቋ ጥናት ተቋሞች በዚህ ጉዳይ ላይ ከመጠን በላይ ርብርብ በማድርግ ብሔራዊ ግዴታቸውን መወጣት ኣለባቸው። የመንግሥት ኣካላትም ይህንን ጉዳይ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት እንዲሁም እራሳቸውን በቀዳሚነት በማሰለፍ የችግሩ ዋና ተፋላሚዎች በመሆን ቋንቋችንን መስመር ለማስያዝ የላቀ ሚና መጫወት ይችላሉ የሚል ከፍተኛ ግምት ኣለኝ።

ዘገባ፣ በኣሁኑ ሰዓት የተሻሻለው የኢትዮጵያ ቃት ማቀነባበርያ በምን ደገጃ ላይ ይገኛል? ሥህስ ኢትዮጵያ ውስጥ ምን ያህል ውጤት ኣስገኝቷል?

ዶ/ር ኣበራ፦ ከዚህ በፊት የሠራኋቸው ኢትዮጵያ ውስጥ ጥሩ ተቀባይነት ኣግኝተው ወደ ፼ (10ሺ) ኮፒ ሸጫለሁ። የጀመርኩትን እየቀናነሱና እየቆራረጡ ሲሸጡ የነበረው ዓይነቱ በዝቶ ገበያው ሲጠፋ በነፃ ማደል ስለጀመሩ ፈረንጆች ገብተውበት በእንግሊዝኛ ኣጻጻፍ ዓይነት ኣንዳንዱን የዓማርኛ ፊደል ከሁለት መርገጫዎች በላይ የሚጻፍበት ኣቅርበው ሕዝቡን እያጃጃሉት ነው። ኣንዳንድ ኣዳዲስ ነገሮችን የሚሠሩ ሰዎች መብት የሚጠበቀው በፓተንት ሲሆን ኢትዮጵያ ዛሬም የሶፍትዌር ባለቤትነት መብት የማስከበር ሥርዓቱ የለም። የባለጥንት ፊደል ኣገር ወደኋላ መቅረት በተለይ ለፊደሉ የደከምነውን ኣሳፍሮናል። ለግዕዝ የሚጠቅሙ ነገሮችን እየሠራን ያለነው መብቶቻችንን በሌሎች ኣገሮች ፓተንቶች ማስጠበቅ ይኖርብናል።

ዘገባ፣ በኣገራችን የቀን መቍጠሪያ ላይም በግልህ ከፍተኛ ጥናት ኣድርገሃል። ለመሆኑ ግዕዝን በተመለከተ ላለፉት ሦስት ሺህ ዓመታት ያለማቋረጥ ሥራ ላይ የዋለ ብቸኛው የዓለም ቋንቋ ነው ቢባል ማጋነን ይሆናል?

ዶ/ር ኣበራ፦የኢትዮጵያ የቀን መቍጠሪያ የጁልያን ነው እየተባልኩ ትክክል ያልሆነ ነገር መማሬን ኣውቃለሁ። የእየሱስን መወለድ ኢትዮጵያውያን የሰሙት ከሰባት ዓመታት በኋላ ስለሆነ ነው ዓመታቱ ወደኋላ የቀሩትም የሚባለውንም ኣስታውሳለሁ። በምርምሬ እንደደረስኩበት ከሆነ ግን ሮማውያን የኢትዮጵን ቀለንጦስ [12] ዓይነት የቀን መቍጠሪያ በ525 ዓ.ም. ሲቀዱና ለኣዲሱ ቀን መቍጠሪያቸው ጁልያን የሚል ስም ሲሰጡት ነው ሰባት ዓመታት ግድም የጨመሩበት። የግዕዝ ፊደላችን ዕድሜ ሦስት ሺህ ዓመታት ነው የሚሉ ኣሉ። ከክርስቶስ ልደት በፊት 3350 ዓመት ሄኖክ[13] መጽሓፉን በግዕዝ ፊደል ጽፎበታል በማለት የሚያምኑም ኣሉ። ይህ ግዕዝን የመጀሪያው ፊደል ያደርገዋል። ረዥም ዕድሜም የማይሰጡት ቢኖሩም ምርምሬን እንደጨረስኩ ኣንድ ጽሑፍ ለማቅረብ ኣስቤኣለሁ[14]

ዘገባ፣ በሌላ በኩል ወደ 200 የሚደርሱ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የተለያዩ የኣትክልት ዘሮችን ባሕላዊ ስማቸውን ኣዲስ ከተሰጣቸው የሳይንስ ስም ጋር በማዛመድ ኢንተርኔት (የዓለም መረጃ መረብ) ላይ ኣቅርበሃል። ይኸንን ለማድረግ ምን ኣነሳሳህ?

ዶ/ር ኣበራ፦ መሬት በመንግሥት ይዞታ ስር ነው እየተባለ ችግር እየተፈጠረ መሆኑን ሰምቻለሁ። በየዓመቱ ያሉት ዛፎችና የተለያዩ ኣትክልት ይመነጠራሉ እንጂ ስለመተካታቸው ብዙም ኣይሰማም። ከሕንድ ውቅያኖስ የሚነፍሰው ውሃ-ኣዘል ነፋስ የኢትዮጵያ ተራራዎች ላይ ሲደርስ ዝናብ እየሆነ ስለሚወርድ ነው ሰሃራ በረሃ የሆነው። ኢትዮጵያውያን ዛፉን እየመነጠሩና ኣትክልቱን እያጋዩ ይህ ዝናብ ኣፈሩን እየወሰደ ስለሆነ የሚቀረው ድንጋይ ኢትዮጵያንም በረሃ ሊያደርጋት ይችላል። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ለሕይወት ኣስፈላጊ ላልሆኑ እንደ ቡና ዓይነቱ ላይ መመርኮዝ የለበትም። ስለዚህ እኔ ከሞትኩ ሰርዶ ኣይብቀል መቆም ኣለበት። ኣትክልት እኛ ወደውጭ የምንተነፍሰውን መጥፎ ኣየር ወስደው ወደ ውስጥ የምንተነፍሰውን ጥሩ ኣየር ይሰጡናል። ኣፈሩን ዝናብን ጎርፍ እንዳይወስደው ይከላከላሉ። ብዙ ዓይነት መድኃኒቶች ይሰጡናል። ምግብ ናቸው። ስለእያንዳቸው ብዙ የተጠኑና ያልተጠኑ ነገሮች ስላሉ የሳይንስና ያካባቢ ስሞቻቸውንና ጥቅሞቻቸውን ማወቅ ኣለብን። ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ ያሉ ዛፎች ኣሉ። ዕውቀቱ እዲስፋፋ ነው ይኸን ስመ ኢጸዋት[15] ገጽ የጀመርኩት። ኢትዮጵያም ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብዙ ዛፎች መትከል መጀመሩን ስለሰማሁ ተደስቻለሁ። ዕድሉ ያለን በምንችለው መርዳት የእግዚኣብሔር ፀጋ የሚቀርብበትን ማዘጋጀት ነው።

ዘገባ፣ ስለሰጠኸን ቃለ ምልልስ ምስጋናችን ከፍ ያለ ነው።

ዶ/ር ኣበራ፦ እኔም ለተሰጠኝ ዕድል ኣመሰግናለሁ።


ዋቤ

1. Abstract, 1978

2. ኤድስ

3. Understanding AIDS, 1988

4. ኢትዮፒክ.ኮም, 1996

5. ግዕዝ በኮምፕዩተር

6. Dr, Aberra Molla

7. Fake Ethiopic in Unicode, 1992

8. Advances Made by Ethiopians inthe Computer Technology,1991

9. Ethiopic in Unicode, 2002

10. Ethiopic in Unicode, 1996

11. Ethiopic Numeral Names

12. The Ethiopic Calendar, 1994

13. ሄኖክ Enoch

14. The Ethiopic Alphabet

15. ስመ እጸዋት


ዘገባ፣ በላስ ቬጋስ፣ ኔቫዳ ለሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በዓማርኛ እየታተመ የሚታደል ነው።

ዘገባ፣ 10ኛ ዕትም፣ ሚያዝያ – ግንቦት፣ ፪ ሺ ዓ.ም. ገጽ 14-18

The above is a published Amharic version of an interview Dr. Aberra Molla gave to reporter Demissie Agonafir of Zegeba.

Zegeba is a free informative publication for Ethiopian residents of Las Vegas, Nevada.

10th Edition, pages 14-18, April – May, 2008

ዶ/ር ኣበራ ሞላ


2/24/08

ሚያዝያ ፳፭ ቀን ፳፻ ዓ.ም. 5/3/2008

error: Content is protected !!